የብፁዕ ወቅዱስ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሌዎ 14ኛ 59ኛው የዓለም ሰላም ቀን መልእክት

ሪያ አልባ እና ትጥቅ አስፈቺሰላም

“ሰላም ለእናንተ ይሁን!”

ይህ ጥንታዊ ሰላምታ ዛሬም በብዙ ባሕሎች ውስጥ የተለመደ፣ በፋሲካ ምሽት ከሙታን በተነሣው በኢየሱስ አንደበት አዲስ ሕይወት የተዘራበት ነው።  “ሰላም ለእናንተ ይሁን” (ዮሐንስ 20፡19፣ 21) የሚለው ቃሉ ሰላምን የሚመኝ ብቻ ሳይሆን፣ በተቀበሉት ሰዎች ውስጥ እና በውጤቱም በሁሉም እውነታ ውስጥ ዘላቂ ለውጥን በእውነት የሚያመጣ ነው። በዚህ ምክንያት፣ የሐዋርያት ተተኪዎች ጳጳሳት በየቀኑ በዓለም ዙሪያ ሁሉ ለዚህ እጅግ ከፍተኛ ለውጥ ድምጽ ይሰጣሉ፡ “ሰላም ለእናንተ ይሁን!” የሮም ጳጳስ ሆኜ ከተመረጥኩበት ምሽት ጀምሮ፣ የራሴን ሰላምታ ከዚህ ታላቅ አዋጅ ጋር ማዋሃድ ፈለግሁ። እናም ይህ ከሙታን የተነሣው የክርስቶስ ሰላም እንደሆነ ደግሜ መግለጽ እፈልጋለሁ – መሣሪያ አልባ እና ትጥቅ አስፈቺ፣ ትሁት እና ጽኑ የሆነ ሰላም።  ሰላም የሚመጣው ሁላችንንም ያለ ቅድመ ሁኔታ ከሚወደን ከእግዚአብሔር አምላካችንና አባታችን ነው።

ከሙታን የተነ የክርስቶስ ሰላም

ሕይወቱን ስለ በጎቹ አሳልፎ የሚሰጠው እና ከዚህ መንጋ ያልሆኑ ሌሎች በጎች ያሉት መልካሙ እረኛ (ዮሐንስ 10፡11፣16 ይመልከቱ)፣ ሞትን ድል ያደረገ እና የሰው ልጅን የሚለያየውን የጥላቻ ግድግዳ ያፈረሰው ሰላማችን ክርስቶስ ነው (ኤፌሶን 2፡14 ይመልከቱ)። የእርሱ መገኘት፣ የእርሱ ስጦታ እና ድል፣ የእግዚአብሔር ሥራ በዓለም ውስጥ በሚቀጥልባቸው በብዙ ምስክሮች ጽናት አማካኝነት ብርሃን መስጠቱን ይቀጥላል፤ ይህም በዘመናችን በሚታየው ጨለማ ውስጥ ይበልጥ ግልጽ እና ደማቅ ይሆናል።

በጨለማ እና በብርሃን መካከል ያለው ልዩነት አዲስ ዓለም ሲወለድ ያለውን የምጥ ስቃይ የሚገልጽ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ምስል ብቻ አይደለም፤ በታሪካዊ ሁኔታዎቻችን ውስጥ በሚገጥሙን ፈተናዎች መካከል እኛን የሚያውከን እና የሚነካን ተሞክሮም ጭምር ነው። ጨለማን ለማሸነፍ፣ ብርሃንን ማየት እና በእርሱ ማመን ያስፈልጋል። ይህ የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት በልዩ እና በተመረጠ መንገድ እንዲኖሩት የተጋበዙበት እና ወደ እያንዳንዱ ሰው ልብ ውስጥ ዘልቆ የሚገባ ጥሪ ነው። ሰላም አለ፤ በእኛ ውስጥም ሊያድር ይፈልጋል። ሰላም ግንዛቤያችንን ለማብራት እና ለማስፋት ልዩ ኃይል አለው፤ ዓመፅን ይቃወማል እንዲሁም ያሸንፋል። ሰላም የዘላለማዊነት እስትንፋስ ነው፡ ለክፋት “ይበቃል” ብለን ስንጮህ፣ ለሰላም ግን “ለዘላለም ይሁን” ብለን እናንሾካሹካለን። ከሙታን የተነሣው ጌታ ወደዚህ አድማስ መርቶናል። በዚህ እምነት በመታገዝ፣ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቼስኮስ “ክፍል በክፍል የሚካሄድ ሦስተኛ የዓለም ጦርነት” ብለው በጠሩት መሃል እንኳን፣ ሰላም ፈጣሪዎች የጨለማውን መስፋፋት መቃወማቸውን ይቀጥላሉ፣ በሌሊትም እንደ ንቁ ዘብ ይቆማሉ።

የሚያሳዝነው ብርሃኑን መርሳትም ይቻላል። ይህ ሲሆን፣ እውነታን የማገናዘብ ስሜታችንን እናጣለን፤ ለጨለማ እና በፍርሃት ለተበላሸ፣ ለከፊል እና ለተዛባ የዓለም እይታ እጅ እንሰጣለን። ዛሬ ብዙዎች ተስፋ የሌለባቸውን፣ የሌሎችን ውበት ለማየት የታወሩትን እና ምንም እንኳን በኃጢአት የቆሰለ ቢሆንም በሰው ልብ ውስጥ ሁል ጊዜ እየሠራ ያለውን የእግዚአብሔርን ጸጋ የረሱ ትርክቶችን “እውነተኛ” ብለው ይጠሩአቸዋል። ቅዱስ አውጉስጢኖስ ክርስቲያኖች ከሰላም ጋር የማይበጠስ ትስስር እንዲፈጥሩ ሲያሳስብ በልባቸው ውስጥ አጥብቀው በመውደድ፣የብርሃኑን ደማቅ ሙቀት በአካባቢያቸው ማንጸባረቅ እንዲችሉ ነው። በአጠገቡ የነበሩትን ሲመክር እንዲህ ብሎ ጽፏል፡- “ሌሎችን ወደ ሰላም ለመሳብ ከፈለጋችሁ፣ መጀመሪያ ራሳችሁ ሰላም ይኑራችሁ፤ በሰላም ጽኑ። ሌሎችን ለማቀጣጠል፣ ነበልባሉ በውስጣችሁ ሊኖራችሁ ይገባል።”

ውድ ወንድሞች እና እህቶች፣ የእምነት ስጦታ ቢኖረንም ወይም እንደጎደለን ቢሰማን፣ ራሳችንን ለሰላም እናዘጋጅ! የማይቻል እና ልንደርስበት የማንችለው ሆኖ እንኳን ቢሰማንም በልባችን እና በሕይወታችን ተቀብለን እና እውቅና እንስጠው። ሰላም ከግብ በላይ ነው፤ ሰላም ሕያው የሆነ የሕይወት ጉዞ ነው። ሰላም በውስጣችን እና በአካባቢያችን አደጋ ላይ በሚወድቅበት ጊዜም እንኳ፣ በማዕበል እንደተከበበች እና ልትጠፋ እንደቀረበች ትንሽ ነበልባል፣ ለእርሱ የመሰከሩትን ሰዎች ስም እና ታሪክ ሳንረሳ ሰላምን ልንጠብቃት ይገባል። ሰላም ምርጫዎቻችንን የሚመራ እና የሚወስን መርህ ነው። ፍርስራሽ ብቻ በቀረበት እና ተስፋ መቁረጥ የማይቀር በሚመስልባቸው ቦታዎች እንኳን፣ ለሰላም ትኩረት የሚሰጡ ሰዎችን አሁንም እናገኛለን። በፋሲካ ምሽት ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱ በፍርሃት እና በተስፋ መቁረጥ ተሰብስበው ወደነበሩበት ቦታ እንደገባ ሁሉ፣ ከሙታን የተነሣው የክርስቶስ ሰላም በምስክሮቹ ድምጽ እና ፊት የተዘጉ በሮች እና መሰናክሎችን ማለፉን ይቀጥላል። ይህ ስጦታ በጎነትን እንድናስታውስ፣ አሸናፊ እንደሆነ እንድናውቅ፣ እንደገና እንድንመርጠው እና ይህንንም በጋራ እንድናደርግ ያስችለናል።

ሣሪ አልባ ሰላም

ከመያዙ ጥቂት ቀደም ብሎ፣ በወዳጅነት ስሜት ውስጥ ሆኖ፣ ኢየሱስ ከእርሱ ጋር ለነበሩት እንዲህ አለ፡- “ሰላምን እተውላችኋለሁ፤ ሰላሜን እሰጣችኋለሁ። እኔ የምሰጣችሁ ዓለም እንደሚሰጥ አይደለም።”  ወዲያውም አክሎ እንዲህ አለ፡- “ልባችሁ አይታወክ፣ አይፍራም” (ዮሐ 14፡27)። ጭንቀታቸው እና ፍርሃታቸው በእርግጥ በቅርቡ ከሚደርስበት ጥቃት ጋር የተያያዘ ነበር። ነገር ግን በጥልቀት ሲታይ ወንጌሎች ደቀ መዛሙርቱን የረበሻቸው የእርሱ ዓመፅ አልባ ምላሽ እንደነበር አልደበቁም፤ ይህ መንገድ ሁሉም፣ በተለይም ጴጥሮስ፣ የተቃወሙበት መንገድ ነበር፤ ሆኖም መምህሩ የእርሱን መንገድ እስከ መጨረሻው እንዲከተሉ ነገራቸው። የኢየሱስ መንገድ ቀላል አለመሆኑ እና ፍርሃት መፍጠሩን ይቀጥላል። በኃይል ሊከላከሉት ለሚፈልጉ ሁሉ እንዲህ ሲል ደጋግሞ ይነግራቸዋል፦ “ሰይፍህን ወደ ሰገባው መልስ” (ዮሐ 18፡11፤ ማቴ 26፡52)። ከሙታን የተነሣው ኢየሱስ ሰላሙ ዓለማዊ መሣሪያ አልባ ነው፣ ምክንያቱም ትግሉ በተጨባጭ ታሪካዊ፣ ፖለቲካዊ እና ማኅበራዊ ሁኔታዎች መካከል የተደረገ መሣሪያ አልባ ትግል ነበርና። ክርስቲያኖች በጋራ ለዚህ አዲስ ነገር ትንቢታዊ ምስክርነት ሊሰጡ ይገባል፤ ይህም ብዙውን ጊዜ ተባባሪ የሆኑባቸውን አሳዛኝ ሁኔታዎች በማስታወስ ነው። የመጨረሻው ፍርድ ታላቅ ምሳሌ፣ ሁሉም ክርስቲያኖች በዚህ ግንዛቤ ውስጥ ሆነው በምሕረትና ርኅራኄ እንዲሠሩ ይጋብዛል (ማቴዎስ 25፡31-46)። ይህን ሲያደርጉ በተለያዩ መንገዶች የሌሎችን ስቃይ ያዳመጡ እና ራሳቸውን ከዓመፅ ማታለያ ነጻ ያወጡ ወንድሞችን እና እህቶችን ከጎናቸው ያገኛሉ።

ምንም እንኳን ዛሬ ብዙ ሰዎች ለሰላም የተዘጋጀ ልብ ቢኖራቸውም፣ ከጊዜ ወደ ጊዜ እርግጠኛ ባልሆነ ዓለም ፊት አብዛኛውን ጊዜ በታላቅ የአቅም ማጣት ስሜት ይሸነፋሉ። ቅዱስ አውጉስጢኖስ ይህንን ልዩ ተቃርኖ አስቀድሞ ጠቁሞ ነበር፡- “ሰላምን ለመያዝ አስቸጋሪ አይደለም፤ ምናልባትም እርሱን ማወደስ የበለጠ ከባድ ነው። ሰላምን ለማወደስ አስፈላጊው ተሰጥኦ እንደሌለን ሆኖን ሊሰማን ይችላል፤ ትክክለኛ ሐሳቦችን እንፈልጋለን፣ ቃላቶቻችንንም እንመዝናለን። ነገር ግን ሰላም እንዲኖረን፣ እዚያው የምንደርስበት ቦታ አለ፣ እናም ያለ ጥረት ልንይዘው እንችላለን።”

ሰላምን እንደ ሩቅ ምኞት በምንመለከትበት ጊዜ እንቅፋት መሆኑ ሲከለከል ወይም በስሙ ጦርነት ሲታወጅ ምንም ላይመስለን ይችላል። እነዚያ “ትክክለኛ ሐሳቦች”፣ በደንብ ሚዛናቸውን የጠበቁ ቃላት እና ሰላም ቅርብ መሆኑን ለመናገር አቅም የጎደለን ሆነን እንታያለን። ሰላም የሚኖርበት፣ የሚለማ እና የሚጠበቅ እውነታ ካልሆነ፣ ጠብ አጫሪነት ወደ ግል እና የሕዝብ ሕይወት ሊስፋፋ ይችላል። በዜጎች እና በገዥዎች መካከል ባለው ግንኙነት፣ ለጦርነት በቂ ዝግጅት አለማድረግ፣ ለጥቃቶች ምላሽ አለመስጠት እና ለዓመፅ በዓመፅ አለመመለስ እንደ ስህተት ሊቆጠር ይችላል። ከሕጋዊ መከላከያ መርህ ባሻገር፣ እንዲህ ዓይነቱ የግጭት አመክንዮ አሁን የዓለምን ፖለቲካ ተቆጣጥሮታል፣ አለመረጋጋትን እና ያልተጠበቁ ሁኔታዎችን በየቀኑ ያባብሳል። ተደጋጋሚ ወታደራዊ ወጪን የመጨመር ጥሪዎች እና ተከትለው የሚመጡት ምርጫዎች፣ በብዙ የመንግሥት መሪዎች ለውጫዊ ስጋቶች እንደ ትክክለኛ ምላሽ መቅረባቸው በአጋጣሚ አይደለም። ወታደራዊ ኃይል የመግታት አቅም፣ በተለይም የኒውክሌር ኃይል የመግታት ሐሳብ፣ በአገራት መካከል ባለው ግንኙነት ምክንያታዊነት የጎደለው አስተሳሰብ ላይ የተመሠረተ ነው፤ ይህም በሕግ፣ በፍትህ እና በመተማመን ላይ ሳይሆን በፍርሃት እና በኃይል የበላይነት ላይ የተገነባ ነው። ቅዱስ ዮሐንስ 23ኛ በዘመናቸው እንደጻፉት፣ “በመጨረሻም ሰዎች የማያቋርጥ ፍርሃት ውስጥ ይኖራሉ። በማንኛውም ጊዜ መጪው ማዕበል በአሰቃቂ ሁኔታ ሊወርድባቸው እንደሚችል ይሰጋሉ። ለፍርሃታቸውም በቂ ምክንያቶች አሏቸው፣ ምክንያቱም በእርግጠኝነት የዚህ ዓይነት መሣሪያዎች እጥረት የለም። ማንም ሰው ጦርነት የሚያስከትለውን አሰቃቂ እልቂት እና ጥፋት የመጀመር ኃላፊነት ለመውሰድ ይደፍራል ብሎ ማመን ቢከብድም፣ ባልተጠበቀ አጋጣሚ እና ሁኔታ ቃጠሎው ሊቀሰቀስ እንደሚችል መካድ አይቻልም።”

ከዚህም በላይ፣ የዓለም ወታደራዊ ወጪ እ.ኤ.አ. በ2024 ካለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር በ9.4% መጨመሩ ልብ ሊባል ይገባል፤ ይህም ያለፉትን አሥር ዓመታት አዝማሚያ የሚያረጋግጥ እና አጠቃላይ 2718 ቢሊዮን ዶላር (ወይም ከዓለም አቀፍ ጠቅላላ የሀገር ውስጥ ምርት 2.5%) የደረሰ ነው። በተጨማሪም ለአዳዲስ ፈተናዎች የሚሰጠው ምላሽ በትጥቅ ላይ የሚደረግ ግዙፍ ኢኮኖሚያዊ ኢንቨስትመንትን ብቻ ሳይሆን፣ በትምህርት ፖሊሲዎች ላይም ለውጥን የሚያካትት ይመስላል። የሃያኛውን ክፍለ ዘመን እና በሚሊዮን የሚቆጠሩ ተጎጂዎችን በከባድ መሥዋዕትነት የተገኘ ግንዛቤን ከሚጠብቅ የትውስታ ባሕል ይልቅ፣ አሁን የስጋት አመለካከትን የሚያሰራጩ እና በትጥቅ የተደገፈ የመከላከያ እና የደህንነት ጽንሰ-ሐሳብን ብቻ የሚያበረታቱ የግንኙነት ዘመቻዎችን እና የትምህርት ፕሮግራሞችን – በትምህርት ቤቶች፣ በዩኒቨርሲቲዎች እና በመገናኛ ብዙኃን – እናያለን።

ሆኖም ግን፣ “ሰላምን በእውነት የሚወዱ የሰላም ጠላቶችንም ይወዳሉ።” ስለዚህ ቅዱስ አውጉስጢኖስ ድልድዮችን እንዳናፈርስ ወይም በነቀፋ እንዳንጸና፣ ይልቁንም ማዳመጥን እና ሲቻልም ከሌሎች ጋር መወያየትን እንድንመርጥ መክሯል። ከስልሳ ዓመታት በፊት፣ ሁለተኛው የቫቲካን ጉባኤ በቤተክርስቲያን እና በዘመናዊው ዓለም መካከል ያለው ውይይት አስፈላጊነት እንዳለው ግንዛቤ በመስጠት ተጠናቋል። በተለይም “ጋውዲዩም ኤት ስፔስ” የተሰኘው ሰነድ ትኩረቱን በጦርነት ዝግመተ ለውጥ ላይ አድርጓል፡- “የዘመናዊ ጦርነት አደጋዎች፣ በቅርብ ጊዜ የተቀቁ የጦር መሣሪያዎች ያላቸውን ሰዎች እንደነዚህ ያሉ ወንጀሎችን የመፈጸም አደጋ ላይ የሚጥሉ መሆናቸው እና፣ በማይቀለበስ ክስተቶች ሰንሰለት፣ ሰዎችን ወደባሰ የግፍ ድርጊቶች የሚገፋፉ መሆናቸው ነው። ይህ በማንኛውም ጊዜ ለወደፊቱ እንዳይከሰት ለመከላከል፣ የዓለም ጳጳሳት አንድ ላይ ተሰባስበው ሁሉም፣ በተለይም የመንግሥት መሪዎች እና ወታደራዊ አማካሪዎች፣ በእግዚአብሔር እና በመላው የሰው ዘር ፊት ያላቸውን ታላቅ ኃላፊነት ሳያቋርጡ እንዲያስቡ ይለምናሉ።”

የጉባኤ አባቶችን ጥሪ በመድገም በሁሉም ደረጃዎች በጣም ውጤታማው አካሄድ ውይይት እንደሆነ በመቁጠር፣ ተጨማሪ የቴክኖሎጂ እድገቶች እና የሰው ሰራሽ አስተውሎት ወታደራዊ አተገባበር የታጠቁ ግጭቶችን አሳዛኝ ሁኔታ እንዳባባሰው መቀበል አለብን። በፖለቲካ እና በወታደራዊ መሪዎች መካከል የሞት የሽረት ውሳኔዎች ለሰው ሰራሽ “ማሽኖች” መስጠት እየጨመረ በመጣበት ሁኔታ ከኃላፊነት የመሸሽ ዝንባሌ እያደገ መጥቷል። ይህ የስልጣኔ መሠረት የሆኑትን የሰብአዊነት፣ የሕግ እና የፍልስፍና መርሆዎችን ታይቶ በማይታወቅ ልክ እና አጥፊ ክህደትን ያመለክታል። መንግሥታትን ወደዚህ አቅጣጫ የሚገፋፉትን የግል ኢኮኖሚያዊ ጥቅሞች ግዙፍ ክምችት ማጋለጥ አስፈላጊ ነው፤ ነገር ግን ሕሊናን እና ሂሳዊ አስተሳሰብን ካልቀሰቀስን በስተቀር ያ ብቻ በቂ አይሆንም። “ፍራቴሊ ቱቲ” በተሰኘው ጳጳሳዊ መልእክት የአሲዚው ቅዱስ ፍራንቺስኮስ ለዚህ መቀስቀስ እንደ ምሳሌ ያቀርባል፡- “በጥበቃ ማማዎች እና በመከላከያ ግንቦች በተሞላው በዘመኑ ዓለም፣ ድህነት በገጠሩ አካባቢ እየተስፋፋ ሳለ፣ ከተሞች በኃያላን ቤተሰቦች መካከል የሚደረጉ የጨካኝ ጦርነቶች መድረክ ነበሩ። ያም ሆኖ ፍራንቺስኮስ እውነተኛ ሰላምን ወደ ልቡ መቀበል እና በሌሎች ላይ ስልጣን የመያዝ ፍላጎት ራሱን ነጻ ማድረግ ችሏል። ከድሆች አንዱ ሆኖ ከሁሉም ጋር ተስማምቶ ለመኖር ፈለገ።” ይህ ዛሬ እንድንቀጥለው የተጠራንበት ታሪክ ነው፣ ይህም ማለት ለትጥቅ አስፈቺ ሰላም አስተዋፅዖ ለማድረግ ኃይሎችን ማቀናጀት ማለት ነው፤ ይህ ለሰላም ዝግጁነት እና ከወንጌላዊ ትህትና የሚወለድ ነው።

ትጥቅ የሚያስፈታ ሰላም

በጎነት ትጥቅ ያስፈታል። አምላክ ሕፃን የሆነው ምናልባት ለዚህ ሊሆን ይችላል። እስከ ሙታን ዓለም ድረስ ጥልቅ የሆነ መውረድን የሚያሳየው ምሥጢረ ሥጋዌ፣ በወጣት እናት ማኅፀን ውስጥ ይጀምራል፤ በቤተልሔም በረትም ይገለጣል።   መላእክት “ሰላም በምድር” እያሉ ዘመሩ፤ ራሱን መከላከል የማይችል አምላክ በሕፃን መልክ መኖሩን አበሰሩ፤ የሰው ልጅም እርሱን በመንከባከብ ብቻ ራሱ የተወደደ መሆኑን ያውቅበታል (ሉቃ. 2፡13-14)። እንደ ሕፃን እኛን የመለወጥ ኃይል ያለው ምንም ነገር የለም። ምናልባትም ልብን የሚነካው ስለ ልጆቻችን እና እኩል ደካማ ስለሆኑ ሌሎች ሰዎች ማሰባችን ነው (ግ. ሐዋ. 2፡37)። ይህን አስመልክቶ የቀደሙኝ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት እንዲህ ሲሉ ጽፈዋል፡- “የሰው ልጅ ደካማነት፣ በምን ያህል ኃይል እንደሚቆይና እንደሚያልፍ፣ ምን ሕይወት እንደሚሰጥና ምን እንደሚገድል ይበልጥ ግልጽ የማድረግ ኃይል አለው። ምናልባት በዚህ ምክንያት፣ አብዛኛውን ጊዜ አቅማችን ውስን መሆኑን ለመካድ እና ደካማና የቆሰሉ ሰዎችን ለማራቅ እንሞክራለን፡ እነርሱ በግለሰብም ሆነ በማኅበረሰብ ደረጃ የመረጥነውን አቅጣጫ የመጠየቅ ኃይል አላቸው።”

ቅዱስ ዮሐንስ 23ኛ “ሁለንተናዊ ትጥቅ ማስፈታት”ን የደገፉ የመጀመሪያው ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ነበሩ፤ ይህ ደግሞ ሊሳካ የሚችለው በልብ እና በአእምሮ በመታደስ ብቻ ነው። “ፓቼም ኢን ቴሪስ” በተሰኘው ጳጳሳዊ መልእክታቸው እንዲህ ሲሉ ጽፈዋል፡- “ይህ የትጥቅ ማስፈታት ሂደት የተሟላና ፍጹም ካልሆነ፣ እንዲሁም ወደ ሰዎች ነፍስ ዘልቆ ካልገባ፣ የጦር መሣሪያ እሽቅድድምን ማስቆም፣ ወይም የጦር መሣሪያዎችን መቀነስ፣ ወይም በዋናነት ሙሉ በሙሉ ማስወገድ እንደማይቻል ሁሉም ሰው ሊገነዘበው ይገባል። ፍርሃትን እና የጦርነትን ጭንቀት ከአእምሯችን ለማስወገድ ሁሉም ሰው በቅንነት መተባበር አለበት። ነገር ግን ይህ በዛሬው ዓለም ሰላም የተመሰረተበትን መሠረታዊ መርሆች ሙሉ በሙሉ በተለየ መርህ መተካትን ይጠይቃል፤ ይኸውም፣ በአገራት መካከል ያለው እውነተኛ እና ዘላቂ ሰላም በእኩል የጦር መሣሪያ ክምችት ላይ ሳይሆን በጋራ መተማመን ላይ ብቻ የተመሠረተ መሆኑን መገንዘብ ነው። ይህ በጋራ የማስተዋል ችሎታ የሚታዘዝ ብቻ ሳይሆን፣ በራሱ እጅግ ተፈላጊ እና የበጎ ነገር ፍሬ ስለሆነ ሊሳካ እንደሚችል እምነት አለን።”

ሃይማኖቶች በስቃይ ውስጥ ላለው የሰው ልጅ ሊሰጡት የሚገባው ታላቅ አገልግሎት፣ ሐሳቦችን እና ቃላትን ሳይቀር ወደ ጦር መሣሪያነት ከመቀየር አዝማሚያ መጠበቅ አለባቸው። ታላላቅ መንፈሳዊ ትውፊቶች እንዲሁም ትክክለኛ ምክንያታዊነት፣ ከደም ትስስር ወይም ከዘር፣ ተመሳሳይ የሆኑትን ብቻ ከሚቀበሉ እና የተለዩትን ከሚገፉ ማኅበራት ወዲያ እንድንመለከት ያስተምሩናል። ዛሬ፣ ይህ በቀላሉ የሚገኝ ነገር እንዳልሆነ እናያለን። እንደ አለመታደል ሆኖ የእምነትን ቋንቋ ወደ ፖለቲካዊ ውጊያዎች መጎተት፣ ብሔርተኝነትን ማበረታታት፣ እንዲሁም በሃይማኖት ስም ዓመፅን እና የትጥቅ ትግልን መባረክ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተለመደ መጥቷል። አማኞች እነዚህን ዓይነቶች ቅዱሱን የእግዚአብሔርን ስም የሚያረክሱ ከሁሉም በላይ በሕይወታቸው ምስክርነት በንቃት ማስተካከል አለባቸው። ስለዚህ ከተግባር ጎን ለጎን፣ ጸሎትን፣ መንፈሳዊነትን፣ እና አብያተ ክርስቲያናት እና የሃይማኖቶች ውይይትን እንደ ሰላም መንገዶች እና በትውፊቶች መካከል የመገናኛ ቋንቋ አድርጎ ማዳበር ከመቼውም ጊዜ በላይ አስፈላጊ ነው። በዓለም ዙሪያ፣ “እያንዳንዱ ማኅበረሰብ ‘የሰላም ቤት’ እንዲሆን፣ ጠላትነትን በውይይት እንዴት ማርገብ እንደሚቻል የሚማሩበት፣ ፍትሕ የሚተገበርበት እና ይቅርታ የሚወደድበት ቦታ እንዲሆን” ተስፋ ይኑር። አሁን ከመቼውም ጊዜ በላይ፣ ትኩረት የሚሰጥ እና ሕይወት ሰጪ የሆነ የመጋቢነት የፈጠራ ችሎታን በማሳደግ፣ ሰላም ምናባዊ ብቻ አለመሆኑን ማሳየት አለብን።

በተመሳሳይ ደግሞ ይህ በምንም መልኩ የፖለቲካዊውን ገጽታ አስፈላጊነት ሊቀንስ አይገባም። ከፍተኛ የሕዝብ ኃላፊነት የተጣለባቸው ሰዎች “በዓለም ዙሪያ ባሉ መንግሥታት መካከል የበለጠ ስለ ሰብአዊ ግንኙነቶች ችግር በቁም ነገር ማሰብ አለባቸው። ይህ ማስተካከያ በጋራ መተማመን፣ በድርድር ቅንነት እና ግዴታዎችን በታማኝነት በመወጣት ላይ የተመሠረተ መሆን አለበት። በመጨረሻም ቅን፣ ዘላቂ እና ጠቃሚ ስምምነቶች ሊጀመሩ የሚችሉበት የስምምነት ነጥብ ላይ ለመድረስ የችግሩ መንስኤና ገጽታ መመርመር አለበት።” ይህ ትጥቅ አስፈቺ የዲፕሎማሲ፣ የሽምግልና እና የዓለም አቀፍ ሕግ መንገድ ነው፤ የሚያሳዝነው ግን፣ ሉዓላዊነትን የተሻገሩ ተቋማት ማጠናከር እንጂ ሕጋዊነትን ማሳጣት ባልተፈለገበት በዚህ ጊዜ፣ በከባድ መሥዋዕትነት የተገኙ ስምምነቶች ተደጋግመው በመጣሳቸው ምክንያት ይህ መንገድ እየተዳከመ ነው።

በዛሬ ዓለም አቀፍ የኃይል ሚዛን መዛባት ምክንያት ፍትሕ እና ሰብአዊ ክብር አስደንጋጭ አደጋ ላይ ናቸው። በዚህ ሰላም እና መረጋጋት ማጣት እና ግጭት ውስጥ እንዴት መኖር እና ራሳችንን ከአደጋ ነጻ ማውጣት እንችላለን? “ተለዋዋጭ ሁኔታዎቹ ከሰው ፈቃድ ውጪ በሆኑ ስም የለሽ እና ግላዊ ባልሆኑ ኃይሎች ወይም መዋቅሮች የተፈጠሩ እስኪመስል ድረስ፣ ዕድልን አሜን ብሎ የመቀበል አገላለጾች” እንዳይስፋፉ በመከላከል፣ ተስፋን ሕያው የሚያደርጉትን እያንዳንዱን መንፈሳዊ፣ ባሕላዊ እና ፖለቲካዊ ተነሳሽነት ማበረታታት እና መደገፍ አለብን። ምክንያቱም፣ እንደተጠቆመው፣ “ሰዎችን ለመቆጣጠር እና በእነሱ ላይ የበላይነት ለማግኘት ዓይነተኛ መንገድ፣ የተወሰኑ እሴቶችን በመጠበቅ ሽፋን ተስፋ መቁረጥን እና ልበ-ቢስነትን ማሰራጨት ነው።” ይህንን ስልት ለመመከት፣ በሲቪክ ማኅበራት ውስጥ ራስን ማወቅን፣ ኃላፊነት የሚሰማቸው የማኅበራት ዓይነቶችን፣ የሰላማዊ ተሳትፎ ልምዶችን፣ እና በአነስተኛም ሆነ በሰፊ ደረጃ የመልሶ ማቋቋም ፍትሕ ልምዶችን ማሳደግ አለብን። ሌዎ 13ኛ ይህንን “ሬሩም ኖቫሩም” በተሰኘው ጳጳሳዊ መልእክታቸው ላይ በግልጽ አስቀምጠዋል፡- “የራሱን ድክመት በማስተዋል የሰው ልጅ የሌላውን ኃይል የውጭ ድጋፍ እንዲጠይቅ ይገፋፋዋል። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እንዲህ እናነባለን፡‘ከአንድ ይልቅ ሁለት መሆን ይሻላል፤ ለድካማቸው ደመወዝ አላቸውና። ቢወድቁ አንዱ ባልንጀራውን ያነሳዋልና፤ አንዱ ግን ብቻውን ወድቆ የሚያነሳው በሌለ ጊዜ ወዮለት’ (መክ. 4፡9-10)። እንዲሁም፡- ‘በወንድሙ የሚረዳ ወንድም እንደ ጠንካራ ከተማ ነው’ (ምሳ.18፡19)።”

ይህ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎችን ራሳቸውን እንደ ነጋድያን እንደገና እንዲያገኙ እና ያንን የልብ፣ የአእምሮ እና የሕይወት ትጥቅ ማስፈታት በውስጣቸው እንዲጀምሩ ያነሳሳው ‘የተስፋ ኢዮቤልዩ’ አንዱ ፍሬ ይሁንልን። እግዚአብሔርም ተስፋዎቹን በመፈጸም ለዚህ በእርግጥ ምላሽ ይሰጣል፡- “በአሕዛብ መካከል ይፈርዳል፥ በብዙ አሕዛብም ላይ ይበይናል፤ ሰይፋቸውንም ማረሻ ጦራቸውንም ማጭድ ለማድረግ ይቀጠቅጣሉ፤ ሕዝብ በሕዝብ ላይ ሰይፍ አያነሣም፥ ሰልፍም ከእንግዲህ ወዲህ አይማሩም። የያዕቆብ ቤት ሆይ፥ ኑ፥ በእግዚአብሔር ብርሃን እንሂድ” (ኢሳይያስ 2፣ 4-5)።

ከቫቲካን፣ ኅዳር 29፣ 2018 ዓ.ም.

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሌዎ 14ኛ

Saint of the day

“በነፃ የተቀበላችሁት በነፃ ስጡ”

ማቴዎስ 10፡7-15

አስተንትኖ፡ የሚስዮናዊ ደቀመዝሙርነት ራስን መቻልን፣ መተማመንን እና ልግስናን ይጠይቃል። የተላክነው ለጥቅም ሳይሆን የምስራቹን ቃል ለማወጅና ለመባረክ ነው።

    The Catholic Bishops Conference of Ethiopia (CBCE)
  • Wawel Street, Besides of Catholic Cathedral, Piassa
  • CBCE@cbce-gs.org
  • scpr@eccsdco.org
  • +251-11-1550300