የአመስያ አባል ሀገራት ተወካዮች የተገኙበት ህገወጥ የሰዎች ዝውውር እና ስደትን መቀነስ ላይ ያተኮረ አውደ ጥናት ተካሄደ

የምስራቅ አፍሪካ የጳጳሳት ጉባኤ ህብረት (AMECEA) አባል ሀገራት የፍትህና ሰላም እና የስደት እና ከስደት ተመላሾች አስተባባሪዎች ተገኝተዋል። ስልጠናው ህገወጥ የሰዎች ዝውውርን እና ህገወጥ ስደትን ለመቀነስ በመደረግ ላይ ያለውን የጋራ ጥረት ለማጠናከር ከሀምሌ 14 እስከ 18 ቀን 2017 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ጎተራ በሚገኘው የቅዱስ ዶን ዶስኮ የሱባኤ ማዕከል ተካሂዷል።
በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን አስተናጋጅነት የተካሄደው ይህ ስልጠና እየተባባሰ ያለውን ህገወጥ የሰዎች ዝውውር ጋር የሚደረገውን ትግል የአባል ሀገራቱ የመንፈሳዊ አጀንዳ አካል ለማድረግ ያለመ ነው።
ተሳታፊዎቹ በቆይታቸው በሀገራቸው ውስጥ ያሉ ተጨባጭ ሁኔታዎችን በጥልቀት በመመርመር እና በህገወጥ የሰዎች ዝውውር ላይ ያለውን ሰፊ እይታ መቃኘት መቻላቸው ተገልጿል። ተሳታፊዎቹ ሀገራዊ እና ክልላዊ ጉዳዮችን ለይተዋል፣ በተግባር የሚታዩ ጣልቃገብነቶች ገምግመዋል እንዲሁም ወደፊት ለመራመድ የሚያስችሉ እና መሻሻል የሚገባቸውን ምክረ ሃሳቦች ሰጥተዋል።
በቆይታቸው ወቅት፣ የAMECEA ቡድን ከክቡር ካርዲናል ብርሃነየሱስ፣ የአዲስ አበባ ሊቀ ጳጳስ እና የኢትዮጵያ ካቶሊክ ጳጳሳት ጉባኤ ፕሬዝዳንት፣ ከክቡር አቡነ ተስፋ ሥላሴ፣ የአዲስ አበባ ረዳት ጳጳስ፣ እና ከክቡር አባ ከተማ አስፋው፣ ዋና ጸሐፊ፣ እና ከጉባኤያቸው ሰራተኞች ጋር የክብር ስብሰባ አድርገዋል።

በቆይታቸውም ከብፁዕ ካርዲናል ብርሃነየሱስ ሊቀ ጳጳሳት ዘካቶሊካውያን እና የኢትዮጵያ ካቶሊክ ጳጳሳት ጉባኤ ፕሬዝደንት፣ ብፁዕ አቡነ ተስፋሥላሴ የአዲስ አበባ ረዳት ጳጳስ፣ ክቡር አባ ከተማ አስፋው ጠቅላይ ጸሐፊ እና የጉባኤው ሰራተኞች ጋር ጉብኝት እና ውይይት አድርገዋል።
የአመስያ ሁለንተናዊ የሰው ልጅ እድገት ክፍል ሃላፊ የሆኑት ክቡር አባ ጳውሎስ የችግሩን አጣዳፊነት አጽንኦት ሰጥተው፣ “የሰው ልጅ ሕገወጥ የሰዎች ዝውውር አሁን በተለይ በአመስያ ክልል ውስጥ ቀውስ ሆኗል” ብለዋል። ይህ ቀውስ በዘላቂነት የሚያደርሰውን ጉዳት ለጳጳሳት ጉባኤዎች እና ለአብያተ ክርስቲያናት ግንዛቤ መፍጠር እንደሚያስፈልግ ጠቁመው ብዙ አፍሪካውያን ወጣቶች እየተሰቃዩ መሆናቸውን አመልክተዋል። ይህንንም ለመቅረፍ ለስደተኞች የሐዋርያዊ አገልግሎት በመስጠት ረገድ አቅምን ማጎልበት፣ የስደተኞች ማእከላት ተወካይ ካህናት መሾምና በጳጳሳት ጉባኤዎች ውስጥ ዘርፉን የሚያስተባብሩ ክፍሎች እንዲቋቋሙ ጠይቀዋል።
የቀድሞ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቼስኮስ “ህገወጥ የሰዎች ዝውውር ዘመናዊ የባርነት እና የቅኝ ግዛት መንገድ ነው” ማለታቸውን በማስታወስ ክቡር አባ ጳውሎስ “ስደተኞችን ለአገራት ስጋት በማድረግ እንዳንፈራ፤ እነዚህ ሰዎች ዋጋ፣ መክሊት አላቸው፣ አብርሃምን የጎበኘው እንግዳ ወደ ቤቱ በረከትን እንዳመጣ ሁሉ ስደተኞችም ለሀገራት የሚያመጡትን ዋጋ እና መክሊት መመልከት ይገባል” ብለዋል።

ክቡር አባ ጳውሎስ የአውደ ጥናቱ መሪ ሃሳብ ከኢዮቤልዩ “የተስፋ አመት” ጋር በማያያዝ በጥቅምት ወር 2018 ዓ.ም. የስደተኞች ኢዮቤልዩ እንደሚከበር ጠቁመዋል። ይህ መሪ ሃሳብ ህገ-ወጥ የሰዎች ዝውውርን ለማስቀረት እድል እንደሚፈጥር አጽንኦት ሰጥተዋል።
በውይይታቸው ዘርፉን በፕሮግራማዊ ተሳትፎ፣ ፖሊሲዎች እና ማዕቀፎች በሀገር አቀፍ፣ በክልላዊ፣ በአህጉር እና በአለምአቀፍ ደረጃ ተዳሰዋል። በህገ-ወጥ የሰዎች ዝውውር ላይ ውጤታማ ዕርምጃዎችን የሚያደናቅፉ ወቅታዊ ክፍተቶችን እና የተበታተኑ አሠራሮችን መፍታት ትኩረት የሚሻ ጉዳይ መሆኑን የገለጹት የሥልጠናው ተሳታፊዎች ለሕገ-ወጥ የሰዎች ዝውውር መስፋፋት መንስኤ የሆኑትን ምክንያቶች በጥልቀት ተወያይተው የተሻሻለ የትብብር አማራጮችን ማስቀመጥ ችለዋል። ሥልጠናው ህገወጥ የሰዎች ዝውውርን ለመዋጋት ዘርፈ ብዙ አካሄዶችን በማጉላት በበርካታ ቁልፍ የውሳኔ ሃሳቦች ተጠናቋል።
