የኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን በአዲስ አበባ ሜትሮፖሊታን ሊቀ ጳጳሳት ሹመት እና በሥልጣን ሽግግር ዙሪያ የሰጠችው መግለጫ

አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ – ሰኔ 12 ቀን 2018 ዓ.ም. – የኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን የጳጳሳት ጉባኤ በአዲስ አበባ ሜትሮፖሊታን ሊቀ ጳጳሳት ሹመት እና በሥልጣን ሽግግር ዙሪያ የተከናወኑ ለውጦችን አስመልክቶ ይፋዊ መግለጫ አውጥቷል።
በካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን የውስጥ አስተዳደር እና የቀኖና ሕግ ድንጋጌዎች መሠረት፣ ቀደም ሲል በአዲስ አበባ ሊቀ ጳጳስነት ሲያገለግሉ የነበሩት ብፁዕ ካርዲናል ብርሃነየሱስ ደምረው ሱራፌል (ዘማኅበረ ልዑካን) በእድሜ ምክንያት በቤተክርስቲያን ውስጥ ካላቸው አስተዳደራዊ ሀላፊነት ነፃ እንዲሆኑ ባቀረቡት ጥያቄ መሠረት ሥልጣን ባለው የቤተ ክርስቲያን አካል ውሳኔ፣ ብፁዕ አቡነ ተስፋሥላሴ (ተስፋዬ) ታደሰ ገብረስላሴን (ዘማኅበረ ኮምቦኒ) የአዲስ አበባ ሜትሮፖሊታን ሊቀ ጳጳሳት አድርጋ መሾሟን አስታውቃለች።
ከዚህ የአገልግሎት ሀላፊነት ጋር በተያያዘ፣ ለአዲሱ ሊቀ ጳጳስ ከኃላፊነቱ ጋር የተያያዙ ሕጋዊ ሥልጣኖችን፣ ተግባራትን እና አስተዳደራዊ ኃላፊነቶችን በሂደት እንደሚተላለፉ ተገልጿል። ይሁን እንጂ ብፁዕ ካርዲናል ብርሃነየሱስ ደምረው ሱራፌል በአለም አቀፍ ካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን እና በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን ባላቸው ቀጣይ ኃላፊነቶች፣ ለተተኪው ሊቀ ጳጳስ እስከሚያስረክቡ ድረስ በኃዋሪያዊ አስተዳደር፣ በመንግሥት መሥሪያ ቤቶች እና በሌሎች የውክልና ሥራዎች የነበራቸው ኃላፊነት ቤተ ክርስቲያኒቱ በይፋዊ መግለጫ እስክታሳውቅ ድረስ የሚጸና መሆኑ እየገለጽን፤ የኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን የጳጳሳት ጉባኤ፣ ብፁዕ ካርዲናል ብርሃነየሱስ ደምረው ሱራፌል በሀገርና በአለም አቀፍ ደረጃ ላበረከቱት ታላቅ አስተዋጽኦ ከፍተኛ አክብሮት አላት። ብፁዕ ካርዲናል በመንግሥት፣ በሲቪል ማኅበረሰቦች እና በህዝብ ዘንድ ያላቸውን ከፍተኛ ተቀባይነትና ክብር ግምት ውስጥ ታስገባለች፤ መንግስትና የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ምስጋናቸውንና እውቅናቸውን መግለጽ ለሚፈልጉ ቤተክርስቲያኒቱ ለመተባበር ዝግጁ ናት፡፡
በተጨማሪም በቤተክርስቲያን ህግ መሰረት በካርዲናልነት ያላቸው መንፈሳዊ አገልግሎትና ሚና 80 ዓመት እስከሚሞላቸው የሚቀጥል ይሆናል፡፡ ቤተክርስቲያናችን ለብፁዕ አባታችን እድሜና ጤና እንዲሰጥልን ትጸልያለች በረከታቸው ይደርብን፡፡
የኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን ለሀገራችን ዘላቂ ልማት ያላትን ቁርጠኝነት ዳግም የምታረጋግጥ ሲሆን፤ በኢትዮጵያ ሰላም፣ አንድነት እና የሁለንተናዊ የሰው ልጆች እድገትን ለማስፈን ከኢትዮጵያ መንግሥት፣ ህብረተሰቡን ከሚያገለግሉ የባለ ድርሻ አካላትና ከሁሉም የሃይማኖት ተቋማት ጋር በጋራ ለመሥራት ያላትን ዝግጁነት ትገልጻለች።
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ!
የኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን የጳጳሳት ጉባኤ
የኮሙኒኬሽን ቢሮ
የሚዲያ ግንኙነት፦ የኮሙኒኬሽን ቢሮ ስ. ቁ. 0922851076 የኢሜይል አድራሻ bezawit.a@eccsdco.org
